ከኢትዮጵያ PEN- Plus ፕሮጀክትን ተግባራዊ የሚያደርገው ማቲዎስ ወንዱ _ የኢትዮጵያ ካንሰር ሶሳይቲ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ወንዱ በቀለ  የፕሮጀክቱን አጠቃላይ ጠንካራና ደካማ ጎን በመገምገም ለቀጣይ ሥራዎች ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር ውይይቱ መካሄዱን ተናግረዋል፡፡ ከኦሮሚያ ክልል በሙከ ጡሪና ከአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት በአዲስ ዘመን የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታሎች የተጀመሩ የሆስፒታሎችን አቅም የማጠናከር ሥራ ለማስፋት መወያየቱ አስፈላጊ መሆኑንም ጠቅሰዋል፡፡

በውይይቱ ላይ የጤና ሚኒስቴር በመወከል የክብር እንግዳ የነበሩት አቶ አዲሱ ወርቁ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ተላላፊ ያልሆኑ ህመሞችን ለመከላከል ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡   ከጤና ጣቢያ ጀምሮ ጥራት ያለው የጤና አገልግሎት መስጠት መቻል አስፈላጊ መሆኑን በማንሳት ማቲዎስ ወንዱ – የኢትዮያ ካንሰር ሶሳይቲ በPEN- Plus ፕሮጀክት በአዲስ ዘመንና ሙከ ጡሪ የጤና አገልግሎቱን ጥራት ክፍ ለማድረግ የሰራቸው ሥራዎች አፈፃፀም  ጥሩ  ነው ብለዋል፡፡
ተላላፊ ያልሆኑ ህመሞችን ለመከላከል የጤና ተቋማትን ደረጃ ከማሻሻል ባለፈ ማህበረሰቡን ማስገንዘብና የባለሙያዎችን አቅም መገንባት ለአገልግሎቱ ዘላቂነት አስፈላጊ መሆኑንም አንስተዋል፡፡

PEN- Plus ፕሮጀክት የዓለም ጤና ድርጅት ህብረተሰቡ ዋና ዋናዎቹን ተላላፊ ያልሆኑ ህመሞች በሚኖርበት አካባቢ ህክምናውን በመከታተል መከላከልና መቆጣጠር እንዲችል በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኘውን የማህበረሰብ ክፍል ማዕከል በማድረግ የተነደፈ ፕሮጀክት መሆኑን የተናገሩት በማቲዎስ ወንዱ _ የኢትዮጵያ ካንሰር ሶሳይቲ የሜዲካል አስተባባሪ ዶ/ር ናትናኤል አለማየሁ ካንሰር፣ የደም ግፊት፣ ስኳር ፣ የልብ ህመም እና የመሳሰሉትን የጤና ችግሮች በተመለከተ የመከላከልና የማከም አገልግሎት ለመስጠት በሁለቱ ሆስፒታሎች ጥሩ ሥራ መሰራቱን ገልፀዋል፡፡

ሶሳይቲው በአዲስ ዘመንና ሙከጡሪ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታሎች የህክምና ማዕክል በመገንባትና የነበረውን በማደስ፣ የህክምና ቁሳቁስ በማሟላት ፣ የመረጃ አያያዝን በማሻሻልና ባለሙያዎችን በማሰልጠን ማህበረሰቡን የሚጠቅም ሥራ በመሰራቱ የሆስፒታሎቹ ተወካዮች አመስግነዋል፡፡