20ኛ ዓመቱን በዚህ ዓመት የሚያከብረው የማቲዎስ ወንዱ የኢትዮጵያ ካንሰር ሶሳይቲ ፕሮጀክቶች አንዱ የሆነው የሳንባ ካንሰር ፕሮጀክት ላለፉት ሦስት ዓመታት  የነበረውን አተገባበር በተመለከተ  ከጤና ሚኒስቴር፣ ከጤና ቢሮዎች እና የፕሮጀክቱ አጋር አካላት ተወካዮች  በተገኙበት በጠንካራ እና ደካማ ጎኖች ላይ ውይይት አካሂዷል፡፡

የሶሳይቲው ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ወንዱ በቀለ የሳንባ ካንሰርን በተመለከተ ከጤና ቢሮዎች እና በጋራ ሲሰሩ ከቆዩ ድርጅቶች ጋር መወያየት ያስፈለገው ተቀናጅቶ ሥራዎችን በተጠናከረ ሁኔታ ማከናወን እንዲቻል መሆኑን ተናግረዋል፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እና የተለያዩ ክልልሎች ጤና ቢሮ ተወካዮች፣ አለርትና ሌሎችም ሆስፒታሎች፣ እንዲሁም ሜሪጆይ እና አምረፍን የመሰሉ ድርጅቶች ተወካዮች ባለፉት ሦስት ዓመታት የሳንባ ካንሰርን በመቆጣጠር እና መከላከል በኩል የማቲዎስ ወንዱ የኢትዮጵያ ካንሰር ሶሳይቲ ትልቅ ድጋፍ አድርጓል ብለዋል፡፡

በሶሳይቲው የፕሮግራም ዳይሬክተር የሆኑት አቶ ዘላለም መንግስቱ ባለፉት ሦስት ዓመታት የተሰሩትን ሥራዎች ሲያብራሩ ማቲዎስ ወንዱ የኢትዮጵያ ካንሰር ሶሳይቲ የሳንባ ካንሰር መንስኤ የሆነውን የትንባሆ ቁጥጥር አዋጅ እንዲወጣ ትልቅ አስተዋፅኦ ማድረጉን አስታውሰዋል፡፡ የሳምባ ካንሰር በተለይ በወንዶች ላይ ሞትን ከሚያስከትሉ የካንሰር ዓይነቶች ቀዳሚው ቢሆንም ህብረተሰቡ ያለው ግንዛቤ አናሳ መሆኑን በመግለፅ ፕሮጀክቱ በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል የሳንባ ካንሰር   የህከምና ቁሳቁስ በማሟላት እና ለአገልግሎት ምቹ በማድረግ እንዲሁም በማሀበረሰቡ ውስጥ ያለውን ግንዛቤ ለማሻሻል ያከናወናቸውን፤ እንዲሁም ለተለያዩ ጤና ተቋማት በቁሳቁስ እና የሰውኃይልን በማብቃት  በፕሮጀክቱ ድጋፍ መደረጉን አብራርተዋል፡፡

 የፕሮጀክቱ ዋና ዓላማ የጤናው ዘርፍ ለሳምባ ካንሰር ምርመራ እና ህክምና ትኩረት እንዲሰጥ ማድረግ መሆኑም ተጠቅሷል፡፡